Saturday, January 31, 2015

የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት ኢትዮጵያ ውስጥ ኖሮ አያውቅም

የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት ኢትዮጵያ ውስጥ ኖሮ አያውቅም

(ecadforum.com ኢዲቶሪያል)

ሰሞኑን ወያኔ/ኢህአዴግ በህግ ተመዝግበው በሀገር ውስጥ የሚንቀሳቀሱ የተቃዋሚ ፖለቲካ ድርጅቶችን ለማጥፋትና በመጪው ምርጫ ላይ እንዳይሳተፉ ለማድረግ በርትቶ እየሰራ መሆኑ ይታወቃል።


እስካሁን መኢሕአድ እና አንድነት ፓርቲ የዚሁ የወያኔ/ኢሕአዴግ የቅድመ ምርጫ “ተቃዋሚዎችን የማዳከም እና የማጥፋት ዘመቻ” ሰለባ ሆነዋል።


በቅርቡ ራድዮ ፋና እና ኢቲቪ ከሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ጋር አድርገውት የነበረውን ቃለ-ምልልስ (በኋላ የቃለ-ምልልሱ ድምጽ ጠፋብን ማለታቸው ይታወሳል፣ ይሁንና ኢሳት ቴሌቪዥን ጠፋ የተባለው ቃለ-ምልልስ በእጁ ገብቶ ኖሮ እያሰራጨው ይገኛል) ቃለ-ምልልሱን ለማዳመጥ እዚህ ይጫኑ። ከቃለ-ምልልሱ መረዳት እንደሚቻለው ፖሊስ ቀመሱ የወያኔ/ኢሕአዴግ ጋዜጠኛ ምን ያህል ሰማያዊ ፓርቲን የሚያስወነጅሉ ነገሮች ፍለጋ ይባዝን እንደነበር ነው። ይህ የሚያመለክተው ሰማያዊ ፓርቲ ቀጣዩ የወያኔ/ኢህአዴግ “ተቃዋሚዎችን የማዳከም እና የማጥፋት ዘመቻ” ሰለባ እንደሚሆን ነው።

ወደ ተነሳንበት ርዕስ ስንመለስ፣ ከላይ የተጠቀሱትን ሁነቶች ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ አንዳንድ በተቃውሞ ጎራ የተሰለፉ ፖለቲከኞች እና ለውጥ አራማጆች “ወያኔ/ኢሕአዴግ የመድበለ ፓርቲ ሥርዓትን እያቀጨጨ ነው፣ ገዢው ፓርቲ የመድበለ ፓርቲ ሥርዓትን እያጠፋ ነው፣ የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት አከተመለት…” ሲሉ ይደመጣሉ።

Friday, January 30, 2015

አንድነትን “እናኝከዋለን፤ እንገድለዋለን” – ምርጫ ቦርድ

ትዕግስቱ አወሉ እንደ አየለ ጫሚሶ

የዛሬ አስር ዓመት “የሕዝብ ሱናሚ” እያለ ሲምል ሲገዘት የነበረው ህወሃት ሱናሚው ወደ እርሱ እየጎረፈ ሲመጣ በረገገ፡፡ መፍትሔ በጠብመንጃ አፈሙዝና በብረት ብቻ እንደሆነ የሚያምነው ህወሃት በረሃ የለመደውን በትሩን አነሳ፤ ንጹሃንን ጨፈጨፈ፤ ደም አፈሰሰ፤ ኢትዮጵያን ወደ እስርቤትነት ቀየራት፡፡ ትዕዛዙን በቀጥታ የሰጡት “ባለራዕዩ” ለፍርድ ሳይቀርቡ “እንደጀመርን እንጨርሰዋለን” ያሉትን ሰፊውን ሕዝብ ሳይጨርሱት እንደ ክዳን ቆርኪ ተስፈነጠሩት፤ ላይመለሱ ሄዱ፡፡
የዛሬ አስር ዓመት የቅንጅት አካሄድ ያስፈራው ህወሃት ጉዳዩን ለራሱ ለፓርቲውና ለሕዝብ ከመስጠት ይልቅ ደም መቃባት ውስጥ ገባ፡፡ ፓርቲው የነበረበት የውስጥ ችግር እንዳለ ሆኖ የፈሪ በትር የዘረጋው ህወሃት የገደለውን ገድሎ ከጨረሰ እና የኢትዮጵያን መሬት በደምና በእናቶች እምባ እንደገና ካጨቀየ በኋላ ቅንጅትን የማፍረስ ተግባሩን በዕቅድ ይዞ በይፋ መንቀሳቀስ ጀመረ፡፡ ግምባር ቀደም ተሰላፊው የተቋም ባንዳ “ምርጫ ቦርድን”፤ በግለሰብ ደረጃ ደግሞ በተለይ ሁለት ግለሰቦችን አሰለፈ፡፡ ዘመቻ “ቅንጅትን መግደል” ተጀመረ፡፡

በወቅቱ የነበረውን ሁኔታ ምንም በማያሻማ ሁኔታ በኢትዮጵያ የቀድሞ የአሜሪካ አምባሳደር የነበሩት ዶናልድ ያማሞቶ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር (ስቴት ዲፓርትመንት) ለሚገኙት አለቆቻቸው “THE ETHIOPIAN GOVERNMENT CHEWS THE CUD” (የኢትዮጵያ መንግሥት ቅንጅትን አኘከው) በሚል ርዕስ የጻፉት እንዲህ ይነበባል፤

Thursday, January 29, 2015

መልእክት አለኝ ለአንድነት አመራሮች እና አባላት

ግርማ ካሳ


የሕወሃት የደህንነት ሃላፊዎች፣ አንድነት መወዳደር የለበትም የሚል ዉሳኔ ካሳለፉ ቆይተዋል። ከዚህ በፊት፣ ፓርቲ እንደ ኢንጂነር ግዛቸው ባሉ ደካማ አመራር ሥር ስለነበረ ፣ የትም ገፍቶ እንደማይሄድ ተረድተው ነበር። ኢንጂነሩ በአባላት ግፊት ከሃላፊነታቸው ተነሱ። አዲስ ፣ ለዉጥ ፈላጊ አመራር መጣ። ችግሩ የአመራር ችግር ስለነበረ፣ አዲሱ አመራር ሃላፊነቱን በያዘ በሶስት ወር ጊዜ ዉስጥ ብቻ፣ የአገሪቷን ፖለቲካ አነቃነቀ። ፓርቲው ተቀባይነቱ ከመቼዉም ጊዜ በላይ አደገ። ይህን ጊዜ አይን ባወጣ መልኩ፣ አይኖቻቸዉን በጨው አጥበው፣ አንድነት ፓርቲ አገዱት። እኔ የምሬ ለነርሱ አዘንኩላቸው !!!! አቤት፣ አቤት፣ አቤት ፣ ……



ነጥብ አንድ። የዛሬው የሕወሃት ዉሳኔ የአንድነቶች የሥራ ዉጤት መሆኑን መረሳት የለበትም። ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ አገዛዙ እንዲዋረድና መሳቂያ እንዲሆን አድርገዉታል። ሕወሃት ጭንቅላት ባላቸው ሰዎች ሳይሆን፣ ፉዞ በሆኑ ሰዎች እየተመራ እንደሆን አለም አውቆታል። የሚቀበሩበትን መቃብር ቆፍረዋል።

Saturday, January 24, 2015

የመኢአድ ም/ፕሬዝደንት ከፍተኛ ድብደባ እንደተፈፀመባቸው ፓርቲው ገለፀ

በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር

የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) የፓርቲያቸው ምክትል ፕሬዝደንት እና የሰሜን ቀጠና ኃላፊ የሆኑት አቶ ዘመነ ምህረት እጅግ ዘግናኝ ድብደባ ደርሶባቸው ሲል ፓርቲው ጥር 15/2007 ዓ.ም በሰጠው መግለጫ አስታወቀ፡፡


አቶ ዘመነ የመኢአድን ጠቅላላ ጉባኤ አድርገው ወደ መኖሪያቸው ጎንደር ከተማ ከተመለሱ በኋላ ከፍተኛ የደህንነት ክትትልና ጫና ይደረግባቸው እንደነበር ለፓርቲያቸው አሳውቀው ነበር ያለው ፓርቲው በ10/05/2007 ዓ.ም ጎንደር ከሚገኘው መኖሪያው ቤታቸው ከባቤታቸውና ከህጻን ልጃቸው ፊት የፖሊስ ልብስ በለበሱ አካላት ከፍተኛ ደብደባ ተፈጽሞባቸው ወዳልታወቀ ቦታ መወሰዳቸውን ግልጾአል፡፡ 

Monday, January 19, 2015

ወከባ እና እስር በህገመንግስቱ እውቅና ይሰጣቸው:: በወከባ እና በእስር ሽብርን በደሃ ህዝብ ላይ መፍጠር ከተጠያቂነት አያድንም::

Minilik Salsawi ምንሊክ ሳልሳዊ)

ይህ የተገፋ ህዝብ እንዳጎነበሰ አይኖርም ቀና ያለ እለት …!!! ወህኒ የጀግና እንጂ የወያኔ እብሪተኞች ቤት አይደለም!!
ባለስልጣናት የጸረ አሸባሪነት ህግን ለማስፈጸምም ይሁን ለመተግበር ሞራላቸው ምን ድረስ እንደሆነ ሊመልሱልን ይገባል:: ተቃዋሚ ፓርቲዎች ያልተመዘገቡ ሀገወጥ እና አሸባሪ ከሆኑ የተወነጀሉበት ተቀባይነት ያለው ክራይቴሪያ ይነገረን እና እናውግዘው:: አጠቃላይ የኢትዮጵያ ህዝቦች ጥያቄያቸው ግልጽ እና ግልጽ ነው ካልሆነ የሚዋከቡበት ምክንያት የለም ካለ ይነገረን እና እናውግዝ ተደጋጋሚ ጸሎት አንፈልግም መንግስታዊ አሸባሪነትን እያወገዝን ወያኔን በትእግስት እየጠበቅናት ነው ይህ ያበጠ ነገር የፈነዳ እለት ወዮላቹ…የምትገቡበት አታገኙም:: እንደ ደርግ ባለስልጣናት ወህኒ አንወሽቃችሁም:: ወህኒ እኮ የጀግና እንጂ የወያኔ እብሪተኞች ቤት አይደለም::

Thursday, January 8, 2015

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሣለኝ ደህንነቱ አደጋ ላይ መሆኑ ተገለፀ

በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ክስ ተመስርቶበት የሶስት ዓመት እስር የተበየነበት ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ደህንነቱ አደጋ ላይ መሆኑ የቅርብ ቤተሰቦቹ ገለፁ። 

ጋዜጠኛ ተመስገን፣ በዝዋይ ወህኒ ቤት ኮማንደር ቢኒያም ተብሎ በሚጠራው የወህኒ ቤቱ አስተዳዳሪ ጠዋትና ማታ
ዛቻና ማስፈራሪያ እየደረሰበት እንደሚገኝና በተጨማሪነትም በቀን ለአምስት ጊዜ ያህል ሌሊትን ጨምሮ በሰበብ አስባቡ ከክፍሉ እየተጠራ እንደሚወሰድ የቅርብ ቤተሰቦቹ አስታውቀዋል፡፡ ጋዜጠኛ ተመስገን፣ በኮማንደር ቢኒያም እየተጠራ “እንገልሃለን፣ ከዚህ አንተ ሳይሆን ሬሳህ ነው የሚወጣው” የሚል ዛቻና ማስፈራሪያ እየደረሰበት እንደሚገኝ ተገልጿል።


ዛቻው እና ማስፈራሪያው እየደረሰበት የሚገኘው በቅርቡ ለንባብ ባበቃው “የኢትዮጵያ መንግስት ገመና” በሚለው መጣጥፉ እንደሆነ የቅርብ ቤተሰቦቹ አያይዘው ገልፀዋል።  

Thursday, January 1, 2015

ወያኔ ‹‹ሰማያዊ ፓርቲ የህዝቡን ሰላም ለማደፍረስ ስለሚያደርገው እንቅስቃሴ›› መረጃ ስጡኝ በሚል ለህዝቡ ቅጽ እያደለ ነው

(ነገረ ኢትዮጵያ)

የኮምኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት በተቃዋሚ ፓርቲዎች በተለይም ሰማያዊ ፓርቲ ‹‹በሰላማዊ ሰልፍ ስም የህብረተሰቡን ሰላም ለማደፍረስ እያደረገ የሚገኘውን እንቅስቃሴ በተመለከተ›› መረጃ እንዲሰጡት ለአዲስ አበባ ነዋሪዎች ቅጽ እያከፋፈለ መሆኑ ታወቀ።