Friday, November 7, 2014

እሥሩ ተጧጡፏል፣ አንድነት ምርጫ እንዳይወዳደር አገዛዙ ይፈልጋል


ግርማ ካሳ

ዜጎች መታሰራቸው እየቀጠለ ነው። በተለይም የአንድነት ፓርቲ አባላት (በጎንደር፣ በትግራይ፣ በመቱ፣ በአዲስ አበባ ፣ በወላይታ ….) ። ብዙዎች ከፍተኛ ደብደባ እየደረሰባቸው ነው። ሕወሃት ፣ በሕዝብ እንደተጠላ ስላወቀ የአንድነት ፓርቲ እንዲዳከም ወይም ከምርጫው ዉጭ እንዲወጣ እየሰራ ነው። አንድነት ሊያሸንፈው እንደሚችል ስላወቀ።

የድርጅቶች መተባበር አስፈላጊ በመሆኑ፣ አንድነት ከመኢአድ ጋር ተስማምቶ የቅድመ ዉህደት ስምምነት ፈርሞ ነበር። ሁሉም ነገር አልቆ ነበር። ሆኖም ምርጫ ቦርድ ወይንም አገዝዙ፣ ሕግ ወጥ በሆነ መንገድ ዉህደቱን አስቁሞታል። ይኸው እስከአሁን ድረስ በአቶ አበባው ለሚመራው መኢአድ እውቅና አልሰጠም ብሎ መኢአዶችን ምርጫ ቦርድ እያጉላላቸው ነው።

የአንድነት ፓርቲ በቅርቡ በድርጅቱ ሕገ ደንብ መሰረት፣ አዲስ አመራር መርጦ መንቀሳቀስ መጀመሩም ይታወቃል። ሆኖ ምርጫ ቦርድ/ ሕወሃት ፣ በንድነት ዉስጥ አስርጎ አስገብቷቸው ከነበሩን በአንድነት እንዲራገፉ ከተደረጉት 2፣ 3 ግለሰቦች ጋር በመመካከር፣ እንደገና ለአዲሱ የአንድነት አመራር እውቅና አልሰጠም እያለ ነው። (የዛሬዉን ሰንደቅ ያንብቡ) ምናልባትም መኢአድ እና አንድነት ከምርጫዉ ሊያግዳቸው፣ አሊያም የነርሱን ሰርተፊኬት፣ ቅንጅትን ለአየለ ጫሚሶ እንደሰጠው፣ ለነ ማሙሸትና እና ለነ ዘለቀ ረዲ ሊሰጣቸውም ይችልም ይሆናል።


አገዛዙ እያሰረ፣ ድርጅቶችን እያገደ፣ ሽብርተኞች እያለ ፣ አይኑን በጨው አጥቦ የፊታችን 2007 ምርጫ አሸነፍኩ ማለቱ አይቀርም። የዉጭው አለም ምንም አይለም። (99.9 በመቶ ሲያሸንፉም የዉጭ አለም ያደረገው ነገር የለም) ። ሆኖም ሕዝቡ ግን ወደ አመጽ መሄዱ አይቀሬ ነው። ሕዝቡ ቀንበር በዝቶበታል። ያሉት መረጃዎች እንደሚያሳዩት፣ የኑሮ ዉድነቱ፣ ዘረኝነቱ፣ የባለስልጣናት ጥጋብ ብዙዎችን በጣም እያማረረ ነው። ፖለቲካው በጣም እየከረረ ነው። እነዚህ ሰዎች ተመረጥን ብለው ቢያወጁም ፣ ያለ ምንም ጥርጥር በሕዝባዊ አመጽ መዉደቃቸው አይቀርም። በዚህ ሁኔታ ሕዝቡን ሊገዙ አይችሉም።

የምመርጠው በሰላማዊ ምርጫ ሕዝቡ ፍላጎቱን እንዲያንጸባርቅ ነው። ሕዝቡም ገዢዎችን ተጠያቂ የሚያደርገው በምርጫ ቢሆን ጥሩ ነው ያንን የምርጫ አማራጭ ገዢዎች ከወሰዱበት ህዝቡ ሌላ መንገድ መፈለጉ አይቀርም።

ለዚህ ነው ገዢዎች ልብ እንዲገዙ አሁንም የምመከረው። ምርጫው ፍትሃዊና ነጻ እንዲሆን ማድረግ አለባቸው። «በምርጫ 2007 ጥሩ ነገር አይተናል፣ ከዚያ በኋላ ያለዉን ደግሞ በ2012 ደግሞ እናስተካክለዋለን » የሚል ሐሳብ ዜጎች እንዲኖራቸው ማድረግ አለባቸው። አለበለዚያ 2012 የሚጠብቅ አይኖርም። ዜጎች አገዛዙን እንደ ግራዚያኒ አገዛዝ ቆጥረው ፣ አገዛዙን ለማስወገድ መንቀሳቀስ ይጀምራሉ።

No comments:

Post a Comment