Sunday, September 21, 2014

በጸረ ሽብር ህጉ የሚፈጸመው በደል እንዲቆም ተጠየቀ

በየተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብት አማካሪ ባለሙያዎች የኢትዮጵያ መንግስት የጸረ ሽብር ህጉን ሰብአዊ መብትን ለመደፍጠጥ ከማዋል እንዲቆጠብ አሳሰበ፡፡ ይህ ማሳሰቢያ የመጣው የተለያዩ የሰብአዊ መብት ድርጅቶች ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የሰብአዊ መብት ጥሰትና አፈና እንዳሳሰባቸው መግለጻቸውን ተከትሎ እንደሆነ ተግልጾአል፡፡ ማሳሰቢያ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን የሰብአዊ መብት ጥሰትና በጸረ ሽብር ስም የሚወሰደውን እርምጃም ለመከላከል ያግዛል ተብሏል፡፡

‹‹ችግሩ እየተከሰተ እንደሆነ ከገለጽንበት ከሁለት አመት በኋላም ጸረ ሽብር ህጉ ጋዜጠኞችን፣ ጦማሪያንን፣ የሰብአዊ መብት ተከራካሪዎችንና ተቃዋሚዎችን ሰለባ እያደረገ እንደሚገኝ ሪፖርት እየደረሰን ነው›› ያሉት ባለሙያዎቹ በተለይ በእስር ቤቶች ማሰቃየት፣ ኢሰብአዊ የሆኑ እርምጃዎች እየተፈጸሙ እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡
ባለሙያዎቹ አክለውም ‹‹ሽብር መዋጋት ጠቃሚ ነው፡፡ ነገር ግን ውጤታማ ለመሆን ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብትን በማክበር መከናወን አለበት›› ብለዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የጸረ ሽብር ህጎች በኢትዮጵያ የወንጀል ህግ ውስጥ በግልጸ መቀመጥና መጠቀሚያ መሆን እንደሌለበት መክረዋል፡፡


የኢትዮጵያ መንግስት በጸረ ሽብር ህጉ የታሰሩትን ዜጎች እንዲፈታ፣ የሰብአዊ መብትን እንዲያከብር ያሳሰቡት ባለሙያዎቹ የኢትዮጵያ መንግስት የመደራጀትና የመሰብሰብ መብትና ሌሎች ሰብአዊ መብት ጥሰቶችን ላይ የሚደረገውን የጉብኝት ጥያቄ በአወንታዊ ምላሽ ሊሰጥ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
(ባለሙያዎቹ የተባበሩት መንግስታትም ሆነ ከመንግስታት ገንዘብ የማይከፍላቸው ገለልተኛ እና በፈቃደኝነት የሚሰሩ መሆናቸው ተገልጾአል፡፡)

No comments:

Post a Comment