Thursday, August 21, 2014

አብርሃ ደስታ ሃብታሙ አያሌዉና እና ኤርትራ

 ( ግርማ ካሳ)


ራሱን ግንቦት 7 ብሎ ከሚጠራ ድርጅት ጋር እና ከድርጅቱ ከፍተኛ አመራሮች በመገናኘት ፤ እንዲሁም ከባንክ በትዕዛዝ ብር በመቀበል የግንቦት 7 ተልዕኮና አላማ ለመፈፀም፤ ቁጥራቸው ከ60 በላይ የሆኑ ግለሰቦችን ለዚህ ጥፋት እንዲሰማሩ በማድረግ» የሚል ክስ ነው በወዲ ሃዉዜን/ትግራይ በሆነው አንጋፋ ፖለቲከኛ እና ብሎገር ላይ ክስ የቀረበው። ሌላው አንጋፋና አንደበተ ርትኡ፣ የሚሊዮኖች ድምጽ ንቅናቄ ግብረ ኃይል ሰብሳቢ፣ ሃብታሙ አያሌውም፣ «የግንቦት ሰባት ተባባሪ ነው» በሚል ነው ለመክሰስ ነው ዝግጅት እየተደረገ ያለው።


አብርሃ ደስታ እና ሃብታሙ አያሌው ፣ «ግንቦት ሰባትን ይደግፋሉ» የሚል ክስ ከቀረበባቸው፣ በተዘዋዋሪ መንገድ «ከሻእቢያ ጋር ወዳጆች ናቸው» ማለት ነው። ታዲያ የሻእቢያ ወዳጅ የሆነ ሰው፣ የኤርትራን መገንጠል ተቃዉሞ፣ ወይንም የኢትዮጵያን የባህር በር ባለቤት መከበር እንዳለበት በማስመር ይናገራል ወይ ? እስቲ የጸረ-ሽብርና የአገር ደህንነት ተብዬው ምላሽ ይስጠን !!!
ሁላችንም እንደምናውቀው፣ በኤርትራ በኩል ትግል እናደርጋለን የሚሉ ወገኖች፣ ኢትዮጵያ የባህር በር እንደሚያስፈልጋት ሊናገሩ አይችሉም። በሻእቢያ ሥር እስካሉ ድረስ ቀይ መስመር ተሰምሮላቸዋል። እነ ግንቦት ሰባቶች፣ ኦነጎች ...፣ እርዳታ የሚያገኙጥ ከሻእቢያ ማእከላቼ ደግሞ አስመራ እስከሆነ ድረስ፣ «ኢትዮጵያ የባህር በር ያስፈልጋታል» ብለው የመናገራቸው ነገር ጭራሽ የማይታሰብ ነው።


ዶር ብርሃኑ ነጋ ከቃሊት እሥር ቤት ሆነው የጻፉት አንድ መጽሃፍ ነበር። መጽሀፍ ላይ ባለው የ ኤርትራ ካርታ ፣ ኤርትራ ተቆርጣለች። ሃብታሙ አያሌው የጻፈው መጽሃፍ ላይ በሚታየው የ ኤርትር ካርታ ኤርትራ አልተቆረጠችም። ሃብታሙ አያሌው፣ ምንም እንኳን ሻእቢያና ሕወሃት/ኢሕአዴግ ከመረብ በስተሰሜን እና በስተደቡብ ያለዉን ሕዝብ ከፋፍለው፣ በደም ቢያቃቡትም፣ «ሰላማዊ በሆነ መንገድ፣ ሁለቱም ወገኖች አሸናፊ በሆኑበት መልኩ፣ 

ወንድማማቾችን አንድ ይቻላል» የሚል እምነት ስላለው ነው፣ ኤርትራ ከተቀረው የኢትዮጵያ አካል ጋር የቀላቀላት። ከ23 አመታት በፊት ያለው አስቦ ሳይሆን ፣ ወደፊት የሚሆነው ታይቶት ነው። ታዲያ ይህ አይነት ፖለቲከኛ ነው የሻእቢያ አሽከር ነው ተብሎ የሚከሰሰው ?
ወደ አብርሃ ደስታ ልውሰዳችሁ። በቅርብ ጊዜ ስለ አሰብ የጻፈው አስደናቂ ጽሁፍ ነበር።

 «ጦርነት ፈርተን ግን ሐገራችንን አሳልፈን አንሰጥም» በሚል ርእስ፣ በአደብ ጉዳይ ላይ፣ አብርሃ ደስታ ሲጸፍ « እኛ ጦርነት አንፈልግም። ሕጋዊ ንብረታችን (ወደባችን) በሰለማዊ መንገድ እንዲሰጠን ነው የምንጠይቀው። አዎ! ጦርነት አንፈልግም። ጦርነት አንፈልግም ማለት ግን ጦርነት ከፍተን በሃይል የሌላ ሀገርና ህዝብ ንብረት አንወርም ማለት እንጂ ጦርነት ፈርተን ልአላዊ ግዛታችን (ሃብታችን) ለሌሎች ሃይሎች አሳልፈን እንሰጣለን ማለት አይደለም። ጦርነት አንፈልግም ማለት ጦርነት እንፈራለን ማለት አይደለም። አዎ! ጦርነት ስለማንፈልግ ሌሎች ህዝቦችን አንወርም። ጦርነት ፈርተን ግን እናት ሀገራችን አናስደፍርም» ነበር ያለው።

ታዲያ በምን መሰፍርትና ሚዛን ነው አቶ ሃብታሙ አያሌው እና አቶ አብርሃ ደስታ የ«ሻእቢያ ተላላኪ» የሚሆኑት ? በምን መስፈርት ነው ግንቦት ሰባቶች ሊባሉ የቻሉት ?
«ህወሓት በራሱ ኮ የሻዕቢያ ተልእኮ ለማስፈፀም በሻዕቢያ የተቋቋመ ድርጅት ነው። ህወሓት የመሰረተው ማነው? ሻዕቢያ ነው። ሻዕቢያ መሓሪ ተኽለ (ሙሴ) የተባለ ኤርትራዊ የሻዕቢያ አባል በትግራይ ለሻዕቢያ ሊያግዝ የሚችል ድርጅት እንዲያቋቁም ወደ ኢትዮዽያ ላከ። እነዚህ ህወሓት የመሰረቱ የሚባሉ ሰባት ሰዎች አሰባስቦ እንዲደራጁ አደረገ» ብሎ አብርሃ ደስታ እንደጻፈው፣ ለሻእቢያ ዉስጥ ዉስጡን የሚቆረቀረዉስ ሕወሃት አይደለችንም ? ያ ባይሆን ኖሮ ተሽቀዳድሞ የአልጀርስ ስምምነት ይፈረም ነበርን? ያ ባይሆን ኖሮ አገር ቤት ካሉ ሰላማዊ ተቃዋሚዎች ጋር አልነጋገርም እያሉ፣ የሕወሃት/ኢሕአዴጉ ዳግማዊ መለስ ዜናዊ፣ ኃይለማሪያም ደሳለኝ «ካስፈለገም አስመራ ድረስ እሄዳለሁ» ይሉ ነበርን ?

እርግጥ ነው እነዚህ ሁለቱ አንጋፋ ወጣት ፖለቲከኞች፣ ኢሳት በተሰኘው ሜዲያ ቀርበው ቃለ ምልልስ አድርገዋል። አቦይ ስብሐት ነጋ፣ አምባሳደር ቪኪ ሃደልሰን፣ ፕሮፌሰር ዶናልድ ሌቪን፣ ወንጌላዊ ዳንኤል ጣሰው ..የመሳሰሉትም በኢሳት ቀርበዋል። ታዲያ እነ አባይ ስብሐት ፣ «ኢሳት ላይ ቀረባችሁ» ተብለው ወደ ወህኒ የወረዱበት ሁኔታስ የታለ ?

በአንድ ሜዲያ መቅረብ አንድን ሰው ጥፋተኛ አያሰኘዉም። አንድ ሰው መከሰስ ካለበት፣ ሊከሰስ የሚገባው በቃለ መጠይቆቹ ዉስጥ ባለው ይዘት ነው። አቶ ሃብታሙና አቶ አብርሃ፣ ሲጽፉም ሲናገሩም በግልጽና በአደባባይ እንደመሆኑ «ይሄን ተናገረዋል.. » ተብለው የሚከሰሱበት ነጥብ ይኖራል ብዬ አላስብም። በመሆኑም አገዛዙ ፣ እነዚህ ሰላማዊ ዜጎችን ሽብርተኞች ናቸው ብሎ ማሰሩ የትም አያደርሰውም። ይህ አይነቱ ፍርድ ገምድልነትና ዜጎችን ያለ ከልካይ ማሰርና ማንገላታት መቆም አለበት።

No comments:

Post a Comment