Friday, August 8, 2014

የአማራ ክልል አመራሮች ከግንቦት7 የኦህዴድ ደግሞ ከኦነግ ጋር እያበሩ ነው ሲል አቶ አዲሱ ለገሰ ያዘጋጁትና ለጠ/ሚ አማካሪዎች የተላከው ሰነድ አመለከተ

ነሃሴ ፩(አንድ)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በሰነዱ ላይ ኢህአዴግ የአመራር ችግር እንዳጋጠመው፣ የትራንስፎርሜሽኑ እቅድ አለመሳካቱ እንዲሁም በጋምቤላ ተማኝ መሪ መጥፋቱ ተዝርዝሯል።
በሃምሌ ወር መጨረሻ የተዘጋጀው ሰነድ ግልባጭ ለጠ/ሚኒስትሩ አማካሪዎች ለአቶ በረከት ስምኦን፣ ለአቶ ደስታውና ለአቶ ኩማ ደመቅሳ ተደርጓል።

የቀድሞው ም/ል ጠቅላይ ሚኒስትርና የኢህአዴግ የፖሊሲ ስልጠና ክፍል ሃላፊ የሆኑት አቶ አዲሱ ለገሰ ” የኢህአዴግን ተቃዋሚ ሃይላት ማንኮላሻ አቅም ግንባታ እና የአመራር ግንባታና የትራንስፎርሜሽን ጉዞ፣ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ የፖሊሲ አማካሪዎች የቀረበ የሚለው ባለ 39 ገጽ ጽሁፍ፣ ኢህአዴግ ከላይ እስከታች የአመራር ችግር እንደገጠመው በዝርዝር ያቀርባል።


ጽሁፉ በመግቢያው “አገራችንን በፈጣን ቀጣይነት ያለውና ህዝቡ በየደረጃው ተጠቃሚ የሚሆንበት የእድገት ጉዞ ከድህነት አላቆ በተራዘመ ሂደት ከበለጸጉት አገሮች ጎራ ለማሰለፍ ይህንን ለማድረግ የሚያስችል አላማ፣ ስትራቴጂ ስልቶችና ፖሊሲዎችን መቀየስ ይጠይቃል። በሌላ አነጋገር አቅጣጫውን በትክክል የሚያመላክት መስመር መቀየስ የትራንሰፎርሜሽን ስኬት የመጀመሪያ ቅድመ ሁኔታ ነው።

መስመሩን ለመቀየስ ይህንኑ ማድረግ የሚችል ብቃት ያለው አመራር ይጠይቃል። ኢህአዴግ በዚህ ፈተና ውስጥ ነው።” ብሎአል።

ሰነዱ ” ለአብነትም እነ አቶ መላኩ ፈንታን ማንሳት ይበቃል” ይልና ” ይህን ተከትሎ በአገሪቱ ያሉ አመራሮች ለመቀበል አለመቻላቸው እና የኡመድ ኡቦንግ ሃገር መክዳት፣ በጋምቤላ ክልል ያለው አመራር ታማኝና አስተማማኝ አለመሆኑ፣ የአማራ ክልል አመራሮች ከግንቦት ሰባት ጋር የተያያዘ አመራር መገኘት፣ የኦህዴድ አመራር ከኦነግ ጋር በማበር እና በአማራ ላይ የደረሰውን በደል በቸልታ መመልከት” በማለት ይጠቅስና “በአሁኑ ሰአት በትግራይ ፣ በቤንሻንጉል ጉሙዝ ( የአመራሩ ቸልተኝነት እንደተጠበቀ ሆኖ)፣ በአፋር፣ በሶማሌ እና በሃረሬ ምርጫውን ማሸነፍ የሚችል አመራር ድምጽ የማግኘት እድል አለው” ብአሎል።

ሰነዱ “የትራንስፎርሜሽን ትግል በውል ይጀመራል እንጅ አይጠናቀቅም ቢባልም በስጋት በተቀመጡት ክልሎች አሁንም አፋጣኝ ስራ ካልተሰራ ኪሳራ ሊያመጡ ይችላሉ” ብሎአል። የአመራሩ ደካማነት የትራንስፎርሜሽን ጉዞ ሳይሳካ እንዲቀር አድርጎታል የሚለው ሰነዱ፣ ድርጅቱ ሰዎችን የሚመለምልበትና የሚያሰለጥንበት መንገድም ብዙ ችግሮች ያሉበት በመሆኑ፣ የምልመላ ዘዴውንና የስልጠና መንገዱን እንዲቀይር ይመክራል።

ኢህአዴግን በመሰረቱ አራቱ ድርጅቶች መካከል ያለው ትውውቅ ደካማ በመሆኑ ከከፍተኛ እስከ መካከለኛ አመራር ያሉት በአንድ ማእከል ስልጠና እንዲሰጣቸው እየተደረገ መሆኑንም
ተጠቅሷል። ኢህአዴግ እጅግ በጣም የሚበዛው አባሉ አርሶ አደር በመሆኑ ፣ የፖለቲካ መሪዎችን በብዛት ለመፍጠር አለመቻሉን የሚጠቅሰው ሰነዱ፣ ከእንግዲህ በዩኒቨርስቲዎችና በከተሞች ላይ ትኩረት ተደርጎ ሰዎችን የመፈለጉ ስራ እንዲጀመር ያሳስባል።

No comments:

Post a Comment