Thursday, July 17, 2014

የመከላከያ ሰራዊት አባላት ስርዓቱን በብዛት እየከዱ ነው


ሐምሌ ፲(አስር)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የኢሳት የመከላከያ ምንጮች እንደገለጹት ባለፉት 20 ቀናት ብቻ ከባድሜ ግንባር ከ 107 ያላነሱ ሰዎች ከድተው ወደ ኤርትራ እና ወደ መሃል
አገር አቅንተዋል። ከ15 ቀናት በፊት በባድሜ አካባቢ ሲያጎ በተባለው ቦታ ላይ የሰፈሩ 60 የ 33ኛ ክፍለጦር አባላት በአንድ ሌሊት ሰራዊቱን ጥለው የጠፉ ሲሆን፣ ኤርትራ መድረስና
አለመድረሳቸውን ለማወቅ የተደረገው ጥረት እስካሁን አልተሳካም።
ወታደሮቹ የጠፉት በክፈለጦሩ የተደረገውን ግምገማ ተከትሎ ነው።  ከግምገማው በሁዋላ በየቀኑ ቢያንስ 2 ሰዎች ከተለያዩ ክፍለጦሮች እየጠፉ ወደ መሃል አገርና ወደ ኤርትራ ያመራሉ።

7 አመት ያገለገሉ በርካታ የመከላከያ ሰራዊት አባላት መልቀቂያ ቢያስገቡም፣ መከላከያ ሚኒስቴር ግን ወታደሮቹን ለመልቀቅ እስካሁን ፈቃደኛ አለመሆኑንም ምንጮች ገልጸዋል።  በዚህም የተነሳ
በሰራዊቱ ውስጥ ያለው ውጥረት ተባብሷል። የመከለካያ ሚኒስቴር በቅርቡ በየአገሩ እየዞረ ሰራዊት ለመመልመል ያደረገውም ሙከራም የተፈለገውን ውጤት ሊያመጣ አልቻለም።
ባለፈው ወር መጨረሻ ላይ የ33ኛ ክፍለጦር አባላት ከመቀሌ በተላኩት በኮሎኔል ሃጎስ ገብረማርያም መሪነት እንዲገመገሙ የተደረገ ሲሆን፣ ገምገማውን ተከትሎ  ኮሎኔሉ ሃጎስ በአንድ
ወታደር ተገድለዋል። ምንጮች እንደገለጹት ግምገማ ከመካሄዱ በፊት የእያንዳንዱ ወታደር ክፍል እንዲፈተሽ የተደረገ ሲሆን፣  ኢቻንግ አሊ በተባለ ከጋንቤላ አካባቢ በመጣ ወታደር ማደሪያ
ክፍል ውስጥ መጽሃፍ ቅዱስ ተገኝቷል።  ወታደር ኢቻንግ መጽሀፍ ቅዱስ ለምን እንዳስገና ሲጠየቅ፣ “አባቴ  እንደማስታወሻ የሰጠኝ ነው” በማለት የመለሰ ሲሆን፣ ገምጋሚው ኮሎኔል ሃጎስ ግን
” ይሄ የውትድርና ቦታ እንጅ የሃይማኖት ቦታ አይደለም፣ መጽሃፍ ቅዱስክን ከካምፕ ውስጥ አስወጣ” ብሎ  ትእዛዝ ሰጥቷል።  ወታደር ኢቻንግም መጽሃፍ ቅዱሱን ለማስረከብ ፈቃደኛ ባለመሆኑና
ይህን ካላደረገም  እንደሚታሰር በማወቁ፣  ኮሎኔሉ  ለእረፍት እንደወጣ መሳሪያውን  ከክፍሉ ይዞ በመምጣት በጥይት ደብድቦ ገድሎታል። ወታደር ኢቻንግ ግድያውን ከፈጸመ በሁዋላ  በገዛ መሳሪያው ራሱን አጥፍቷል።
በግምገማው ወቅት ከፍተኛ ትችት የተሰነዘረባቸው 60 የሰራዊቱ አባላት ኮሎኔል ሃጎስ በተገደሉበት እለት፣  ሌሊቱን ተመካክረው በአንድ ጊዜ መጥፋታቸውን ምንጮች አክለው ገልጸዋል።
በባድሜ አካባቢ ያለው እስር ቤት ዋጠው እየተባለ የሚጠራ ሲሆን፣ ጎንና ጎኑ በድንጋይ ተሰርቶ ከስር ስሚንቶ፣ ከስሚንቶው ስር ደግሞ ውሃ እንዳለውና እስረኞችን በቅዝቀዜ ለመቅጣት ተብሎ መዘጋጀቱን
ለማወቅ ትቸሎአል። እስረኛ ወታደሮች ቀኑን ሙሉ ብርሃን ሳያዩ በካቴና እንደታሰሩ እንደሚገረፉ የውስጥ ምንጮች ገልጸዋል።
በሰራዊቱ ውስጥ እየጨመረ የመጣው ተቃውሞ ያሰጋው መንግስት የደሞዝ ጭማሪ እንደሚያደርግ ቃል በመግባት ለማረጋጋት ቢሞክርም፣  ሰራዊቱ ግን አስተዳዳራዊ በደሎችንና በሰራዊቱ ውስጥ ያለውን
ዘረኝነት በመጥላት፣ የደሞዝ ማማለያውን ባለመቀበል ጥሎ እየጠፋ ሲሆን  አንዳንድ ወታደሮች ደግሞ መልቀቂያቸው ከዛሬ ነገ ይደርሳል በማለት በተስፋ እየተጠባበቁ እንደሚገኙ መረጃው አመልክቷል።
ወታደራዊ አዛዦች በአዲስ አበባና በተለያዩ የአገሪቱ ዋና ዋና ከተሞች የገነቡዋቸው ዘመናዊ ህንጻዎችና ያካበቱት የሃብት መጠን በሰራዊቱ ውስጥ ተደጋግሞ የሚነሳ ሲሆን፣ በተለይ ከህወሃት ውጭ ያሉ አንዳንድ
የአማራ እና የኦሮሞ ወታደሮች አመጽ ሊያስነሱ ይችላሉ ተብሎ በመጠርጠራቸው ልዩ ክትትል እንደሚደረግባቸው ምንጮች ገልጸዋል። የጋምቤላ ተወላጅ የሰራዊቱ አባላትም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ታማኝነታቸውን
እያጎደሉ ነው በሚል በአንዳንዶች ላይ ልዩ ክትትል እየተደረገባቸው ነው።
አንድ የመከላከያ ሰራዊት አባል ለአባይ ግድብ ማሰሪያ፣ ለመለስ ፋውንዴሽንና ለሌሎችም የክፍያ ትእዛዞች ገንዘብ ከከፈለ በሁዋላ ተቆራርጦ የሚደርሰው ክፍያ ወር እስከ ወር አያደርሰውም።  በአንጻሩ ነባር
ታጋዮች የሚባሉት የህወሃት ጄኔራሎች በመቶ ሚሊዮኖች ብር የሚቆጠር ህንጻዎችን ገንብተው በማከራየት ላይ መሆናቸው ይታወቃል።

No comments:

Post a Comment