Monday, July 21, 2014

ከድምፃችን ይሰማ የተላለፈ ጥሪ፦ “መንግስታዊው ‘ጥቁር ሽብር’ የህዝብን የድል ችቦ አያጠፋውም!”

ከቀናት በፊት በእለተ ጁምአ በታላቁ አንዋር መስጂድ በመንግስት ታጣቂዎች የተወሰደው ድንበር የለሽ ጭፍጨፋ የሙስሊሙ ህብረሰተብ ሰላማዊ ትግል በታሪኩ ሌላ መጠምዘዣ ውስጥ እንዲገባ ምክንያት እንዲሆን የሚያስገድድ ነው፡፡ በዚህ በመንግስት የደህንነት ኃይሎችና በፖሊስ ሀላፊዎች ከቀናት በፊት ታቅዶ በተወሰደ እርምጃ ከ6 ሺ በላይ የመንግስት ቅጥረኛ ሲቪል ለባሾች እንደተሳተፉበት መገለጹ ይታወሳል፡፡ ቅጥረኞቹ የተከበረው የረመዳን ወር የጁምአ ሰላት ከመሰገዱ በፊት በመስጊዱ ውጫዊ ሰሜናዊ አቅጣጫ ግርግር በማስነሳትና ከፖሊሶች ጋር ከሁለቱም አቅጣጫ ድንጋይ በመወራወር የታለመውን ውጤት ለማምጣት ሞክረዋል፡፡ በዚህም በአካባቢው የነበሩትን ጨምሮ በሁሉም አቅጣጫ የነበሩና በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ሙስሊሞች የጁምአ ሰላታቸውን እንዳይፈጽሙ እክል ከመሆናቸውም በላይ እጅግ በርካታ ጾመኛ ሙስሊሞች ላይ እጅግ አሰቃቂ ጭፍጨፋ ፈጽመዋል፡፡
በእለቱ በተካሄደው ጭፍጨፋ እንደተለመደው የመንግስት የጦር ሜዳ ስልት ሙስሊሙን ከሁሉም አቅጣጫ በቆረጣ ስልት ለሰላት በተቀመጠበት በመቁረጥ በነፍስ ወከፍ በያዙዋቸው ዱላዎችና የመሣሪያ ሰደፎች ርህራሄ አልባ በሆነ ሁኔታ ደብድበውታል፤ ጭፍጨፋ አድርሰውበታል፡፡ ጭፍጨፋው እድሜ፣ ጾታ፣ አስተሳሰብና፣ የአካል ሁኔታን ሳያገናዝብ ነበር የተወሰደው፡፡


ይህን ጭፍጨፋና ክስተቱ የደረሰበትን እለት ማሰብና በሌላ የታሪክ የቀን መቁጠሪያ ውስጥ መክተቱ አስፈላጊ ከመሆኑ አንጻር ለእለቱ ልዩ ስያሜ እንዲሰጠው ታምኖበታል፡፡ በዚህም መሰረት በእለቱ የተወሰደው መንግስታዊ ሽብር ‹‹ጥቁር ሽብር›› የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ ‹‹ጥቁር ሽብር›› በሰለጠነ ውይይት ከማያምን፣ ሰላማዊነትና ዲሲፒሊን ከማይገባው መንግስት የሚፈልቅ፣ ሰዎች ሳይሆኑ ዱላ ብቻ የሚናገርበት፣ ሐሳብ የሚንሸራሸርበት ሳይሆን ነውጥና ግፍ የሚሰፍንበት ሂደት ነው፡፡ ‹‹ጥቁር ሽብር›› አይናቸውን የጋረደው ጥቁር ግርዶሽ የህዝብን እውነታ እንዳይረዱ ያደረጋቸውና ብቃት የሌላቸው ኃላፊዎች የሚወስኑት፣ ሰብዓዊነት በጭካኔ ጭለማ ውስጥ የሚሰጥምበት አስከፊ ክስተት ነው፡፡ አዎን! ለሰላማዊ ሕዝብና ጥያቄ ምላሹን ዱላ ያደረገ ኃይል፣ ባልታጠቀና በእጁ ድንጋይ ባልጨበጠ ጾመኛ ሕዝብ ላይ የጥይት ቃታ የሚስብ መንግስት ከርሞም የሚነዳው በ‹‹ጥቁር ሽብር›› ብቻ ነው፡፡ ሰላማዊ ትግላችንም ከዚህ በኋላ በሚኖረው ሂደት የሐምሌ 11/2006ን አሰቃቂ የመንግስት ጭፍጨፋ የታሪክ ካስማ በማድረግ እለቱ ‹‹ጥቁር ሽብር›› ሲባል ከዚህ በኋላ ያሉ ክስተቶችም ‹‹ከጥቁር ሽብር በኋላ›› ወይም ‹‹ከጥቁር ሽብር በፊት›› እየተባሉ የሚዘገቡ ይሆናል፡፡
‹‹ጥቁር ሽብር›› ከአወሊያ መስጂድ የውድቅት ሰዓት ቀድሞም በአሳሳ በጁሙአ ሰላት ወቅት የተፈጸመ ነው፡፡ ‹‹ጥቁር ሽብር›› ጨለማ ተገን ተደርጎ በአወሊያ መስጂድ ከሁለት አመታት በፊት እንደተወሰደው፣ በጠራራ ጸሐይም በሲቪል ለባሽ ካድሬዎች አሻጥር ተከልሎ ልባቸው በተንኮል በጠቆረ ኃላፊዎች ትእዛዝ፣ በታወረ ህሊና እና አይን የሚወሰድ የአላዋቂነት ድርጊት ነው፡፡ ‹‹ጥቁር ሽብር›› እውቀት አይጠይቅም፤ ዱላና እርግጫ ብቻ ነው የሚጠይቀው፡፡ ‹‹ጥቁር ሽብር›› ህገ መንግስቱን በድቅድቅ ጨለማም ሆነ በቀትር ጸሐይ ንዶ ያሻውን የሚገድል፣ የተቀረውንም የሚያቆስል ጸያፍ ድርጊት ነው፡፡ የእለቱ ስያሜ እስከመቼውም የሚዘልቅ ሲሆን ለወደፊቱም በዚህ የ‹‹ጥቁር ሽብር›› አሻጥር ውስጥ የተሳተፉ ወንጀለኞች ለፍርድ የሚቀርቡበት ጊዜ ሩቅ እንደማይሆን እናምናለን፡፡
ይህ በእውር ድንበር የተወሰደና ማንንም ሳይለይ ድንገት እንደደራሽ ጎርፍ የደረሰ ‹‹ጥቁር ሽብር›› ብዙዎችን በአካል ያቆስል ይሆናል፤ በተቃራኒው ግን ዱላውና ግድያው የሰዎችን ሞራል ከፍ ያደርጋል፡፡ በመብት ነጠቃ የ‹‹ጥቁር ሽብር›› ሰለባነት ማግስት የሞራል ከፍታና የአላማ ጽናት ጎልቶ ይታያል፡፡ ባለፉት ሶስት በሚጠጉ አመታት መሰል በርካታ የ‹‹ጥቁር ሽብር›› ዘመቻዎች ተፈጽውብናል፡፡ በማግስቱ ግን ሁሌም ጎልተን እንታያለን፡፡ በተደበደብን ቁጥር፣ በደሉ ባረፈብን ቁጥር ቁስላችን ከመመርቀዝ ይልቅ እየጠገገ ጥንካሬያችንን ሲያጎላው አይተናል፡፡ ሁላችንም እንደምንረዳው ኃይል የተስፋ መሟጠጥ፣ የሐሳብና ዴሞክራሲያዊነት መራቆት አይነተኛ ምክንያት ነው፡፡ ተስፋ መቁረጥ ሲናኝ ኃይል ባህሪ ይሆናል፡፡ የእኛ ትግል ግን በሰላምና ዲሲፕሊን ውስጥ እያለፈ ድልን ይቀዳጃል!
መንግሥታዊው ‹‹ጥቁር ሽብር›› የህዝብን የድል ችቦ አያጠፋውም!
ትግላችን በአላህ ፈቃድ እስከ ድል ደጃፎች ድረስ ይቀጥላል!
ድምጻችን ይሰማ!
አላሁ አክበር!

No comments:

Post a Comment