Thursday, July 10, 2014

እየነጋ ነው!


  • 45
habtamu ayalew
yeshiwas
DEA54BEE-2996-4145-A17A-2842A121CD0E_w640_r1_s

አብርሃ ደስታአብርሃ ደስታ

አሁን ደግሞ ሀብታሙ አያሌው፣ የሺዋስ አሰፋ፣ ዳንዔል ሺበሽ፣ አብረሃ ደስታን አሰሩ። አንዳርጋቸው ፅጌን የማሠራቸው ዜና ገና አቦሉ ሳይጠጣ እኒህን ደገሙ። ለምን? አጭሩ መልስ እየነጋ ስለሆነ ነው። ኢትዮጵያዊ ሆኖ የእኒህን ታጋዮች ማንነትና ተግባር የማያውቅ የለም፤ ቢያንስ በትግሉ ዙሪያ ያለነው ኢትዮጵያዊያን። ታዲያ መንጋቱ እኮ፤ የአውራ ደሮውን ጩኸት፣ የጎኅን መፈንጠቅ፣ የጨለማውን መገፈፍ ይጠይቃል። ይህ ደግሞ በገዛ ፈቃዱና ቁጭ ብለው ስለጠበቁት የሚሆን አይደለም። የመሬትን በፀሐይ ዙሪያ መሽከርከር ተፈጥሯዊ ግዴታ ተከታይ ነው። በጭቆና የሚማቅቅ ሕዝብ፤ ለነፃነቱ መነሳቱና ከመካከሉ ቆራጦቹ ጧፍ ሆነው ከፊት መቅለጣቸው ግዴታ ነው። ይህ ነው የኒህ ቆራጥ ታጋዮች ሕይወት ትርጉሙ። እንደኛው ቤተሰብ፣ ንብረትና ምቾት አልጠሉም። ለወገንና ለሀገር ሠጡት። የሕይወታቸውን ትርጉም፤ በጣሊያን ጊዜ ከፋሽስቶች ለመጋፈጥ ከየመንደሩ በባዶ እግራቸው፤ ከመላ ኢትዮጵያ ጫፍ እስከጫፍ ወጥተው እንደቀሩት አርበኞቻችን፤ የኔ ሕይወት ለነገዋ ኢትዮጵያ ሕልውና ይሁን ብለው ያለማመንታት፤ ፀረ-ኢትዮጵያ የሆነውን ራሱን የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር ብሎ የሚጠራውን መንግሥት በመቃወማቸው እስር ቤት ገቡ። ከኛ የተለዩ ልዩ ፍጡር ሆነው አይደለም። እንደኛ አባትና እናት፣ እህትና ወንድም፣ አክስትና አጎት፣ ባለቤትና ልጆች ያሏቸው ናቸው። ሰው ናቸው። አርበኛ ያደረጋቸው ተፈጥሯዊ ልዩነታቸው ሳይሆን፤ ለሕይወታቸው የሠጡት ትርጉም ነው። የብዙኀኑን የኢትዮጵያዊያን ሕይወት የኔ ብለው፣ ስቃያቸውን እነሱ ተሸክመው፣ ለሕዝቡ ጭዳ ሆነው ተሰለፉ። እንደነ አንዱዓለም አራጌ፣ እስክንደር ነጋ፣ ርዕዩት ዓለሙ፤ ሰግዶ ማደርን አልፈልግም ብለው፤ አረዓያችን ሆኑ። እንዲነጋ ምን ማድረግ አለብን።

አይቀሬው ንጋት እየመጣ ነው። የኛ ኃላፊነት ብዙና የተቆላለፈ አይደለም። እኒህ ቆራጦች የነገሩን ምንድን ነው? ፍርሃትን፤ ራሱን የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር ብሎ የሚጠራው መንግሥት ቀምቶናል። ከኛ በኩል ፍርሃት ቦታ የለውም። የኢትዮጵያዊያን ጠላት የሆነው ራሱን የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር ብሎ የሚጠራው መንግሥት በፍርሃት ተውጧል። ምስክርነቱ፤ ማንንም የሚፈራውንና በሕዝቡ ዘንድ ተቀባይነት አለው የሚለውን ግለሰብ ሁሉ እያሠረ ነው። እኒህ ጀግኖች የታሠሩት የዚህ ወይንም የዚያ ድርጅት አባል ስለሆኑ አይደለም። ከሕዝቡ ጋር ስለወገኑ ብቻ ነው። ለዚህ ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት፤ ማንኛውም ከሱ ቁጥጥር ውጪ የተደራጀ ክፍል ጠላቱ ነው። እናም የዚህ ወይንም የዚያ ድርጅት አባል መሆን አይደለም የመታሰሪያ ወንጀሉ፤ ከሕዝቡ ጋር የቆመ መሆኑ ብቻ ነው። የሚያስበረግገውና የሚያንቀጠቅጠው የሕዝብ ወገን የሆነ ማንኛውም ድርጅት ነው። ታዲያ ድርጅቶች በሙሉ አንድ ዓላማ እስከያዙ ድረስ፤ ሕዝቡ አሁን ነው ትግሉ ወደፊት መሄድ ያለበት እስካለ ድረስ፣ ንጋቱ በር አያንኳኳ እስከሆነ ድረስ፤ ተልዕኳችንን አንድ አድርገን ሌቱን እናንጋው።
ምንድን ነው የአሁን ጥያቄ? ይፈቱልን ብሎ ልመና አይደለም። ይህ በታሠሩት ቆራጦች ዓይን ጥቃት ነው። ይህን ብናደርግ ለገዥው ቡድን ኩራት ነው። እንኳን ያሠራቸውን ሊፈታ፤ የሚቀጥሉትን ታሳሪዎች እያዘጋጀ ነው። እነሱም ሆኑ መታሠራቸው፤ ጧፍ ሆኖ መንገዱን መሪያችን እንጂ፤ የመንገዱ ማብቂያ አይደለም። ገና የራሱን ጥላ ለማሠር የሚሯሯጥ ጠላት ነው ያለን። አጥንት ቆጠራውን ለገዥው ክፍል እንተውለት። እሱም እንኳ ለአጥንት ቆጠራው ቦታ እንደማይሠጠው አብርሃ ደስታን በማሠር አሳይቶናል። አብርሃ ደስታ በትግራይነቱ፣ ትግሬዎች እየተጠቁ ነው ብሎ የተደራጀ ነበር። አልሆነም። ኢትዮጵያዊነታችንን እንጎናጸፈው። በኢትዮጵያዊነታችን ይኼን ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት እንታገለው። ሁላችንን ሊያስተባብሩን የሚችሉ አራት የትግል ዕሴቶች አሉን።
፩ኛ፤ የኢትዮጵያዊያን ሉዓላዊነት
፪ኛ፤ የኢትዮጵያ ሀገራዊ አንድነት
፫ኛ፤ የእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ዴሞክራሲያዊ መብቶች
፬ኛ፤ በኢትዮጵያ የሕግ የበላይነት
እኒህ ናቸው የታጋዮችን አንድነት የሚጠይቁ የትግል ዕሴቶቻችን። በነዚህ ዙሪያ ሁላችን መጠማጠም አለብን። የየድርጅቶች ታሣሪዎች መሆናችንን ለነፃነቱ ጊዜ እንተወውና፤ ለኢትዮጵያዊያን በሙሉ፣ ለሀገራችን አንድነት፣ በየእስር ቤቱ ለሚማቅቁ ጀግኖቻችንና አሁን በየዕለቱ ለሚታገቱት ቆራጥ ኢትዮጵያዊያን አርበኞቻችን አንድነታችንን እናጠንክር። ይህ ወደ ድል ይወስደናል። እነዚህን ሁሉን አቀፍ የሆኑ አራት ነጥቦች በሚያኩ ዙሪያ ሀገራዊ አጣዳፊ ጥሪዎች ሰሞኑን ድረገፆቻችንን አሙቀውታል። ጥሪዎቻችሁ ወደ መሰባሰቡ እንዲያመራ ፈልጋችኋል በማለት፤ ጥሪዎችን በተደጋጋሚ ያደረጋችሁ ግለሰቦች፤ እኛው ጀማሪዎች እንሁን የሚል ጥሪ በማስቀደም እንድንገናኝ ይኼው በ ( eske.meche@yahoo.com ) እገኛለሁ።

No comments:

Post a Comment